Sep 25, 2014

መስቀሉ የት ነው ያለው? ክፍል ፩

                     "በወንጌሉ ያመናችሁ  እንኳን ለብርሃነ መስቀሉ አደረሳችሁ"                           

በእምነት ታሪክ ውስጥ የታሪክ፣ የአርኬዎሎጂ እና የቅርስ ጥናት ሰዎችን ያስጨነቁ ሁለት ጥያቄዎች አሉ፡፡ ታቦተ ጽዮን እና ጌታ የተሰቀለበት መስቀል የት ነው ያሉት? የሚሉት ጥያቄዎች፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ አሰሳዎች፣ ቁፋሮዎች፣ መዛግብትን የማመሳከር ሥራዎች፣ አሉ የተባሉ የይዞታ ጥያቄዎችን የመመርመር ፍተሻዎች በመካሄድ ላይ ናቸው፡፡ በጣም የሚገርመው ነገር ግን የዓለም ቅርሶች መናኸርያ የሆነችው ኢትዮጵያ ሁለቱንም በተመለከተ ለዓለም የምትገልጣቸው ነገሮች አሏት፡፡
ሰሞኑን በሀገራችን ኢትዮጵያ የመስቀል በዓል በመከበር ላይ በመሆኑ «ለመሆኑ ጌታ የተሰቀለበት መስቀል የት ነው ያለውየሚለውን ጥያቄ በተመለከተ ያሉ መረጃዎችን እንቃኝ፡፡

የመስቀሉ መጥፋት

በአብያተ ክርስቲያናት ከሚነገረው ትውፊት በስተቀር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተሰቅሎት የነበረው መስቀል እንዴት ሊጠፋ እንደቻለ የተመዘገበ ታሪክ እኔ አላገኘሁም፡፡ አብዛኞቹ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት ግን አይሁድ በመስቀሉ ላይ ይደረግ የነበረውን ተአምራት በመቃወም ከክርስቲያኖች ነጥቀው እንደ ቀበሩት ይተርካሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊው አውሳብዮስ የቆስጠንጢኖስ የሕይወት ታሪክ /Life of Constantine/ በተሰኘው መጽሐፉ ላይ በክርስቲያኖች ዘንድ ታላቅ ሥፍራ የነበረው የጌታ መቃብር ተደፍኖ በላዩ ላይ የቬነስ ቤተ ጣዖት ተሠርቶ እንደ ነበር ይናገራል፡፡ አውሳብዮስ በዝርዝር አይግለጠው እንጂ ይህ የቬነስን ቤተ መቅደስ በጎልጎታ ላይ የመሥራቱ ጉዳይ የሮሙ ንጉሥ ሐድርያን 135 ዓም ኢየሩሳሌምን Aelia Capitolina አድርጎ እንደ ገና ለመገንባት የነበረው ዕቅድ አካል ነው፡፡
አይሁድ በሮማውያን ላይ እስከ ዐመጹበት እና ኢየሩሳሌም ከክርስትና በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ እስከ ጠፋችበት እስከ 70 ዓም ድረስ መስቀሉ በክርስቲያኖች እጅ እንደ ነበር ይታመናል፡፡ በኋላ ግን ክርስቲያኖቹ የሮማውያንን እና የአይሁድን ጦርነት በመሸሽ ከኢየሩሳሌም ወጥተው ወደ ሌሎች ሀገሮች ሲሰደዱ፤ በኋላም በባር ኮባ ዐመፅ ጊዜ /132-135 ዓም/ ኢየሩሳሌም ፈጽማ በሮማውያን ስትደመሰስ የመስቀሉ እና የሌሎችም ክርስቲያናዊ ንዋያት እና ቅርሶች ነገር በዚያው ተረስቶ ቀረ፡፡ ንጉሥ ሐድርያንም የኢየሩሳሌም ከተማን ነባር መልክ በሚለውጥ ሁኔታ እንደ ገና ሠራት፡፡ ያን ጊዜ ነው እንግዲህ የቬነስ ቤተ መቅደስ በጌታችን መቃብር ላይ የተገነባው፡፡ ቆስጠንጢኖስ ለኢየሩሳሌሙ ኤጲስ ቆጶስ ለአቡነ መቃርዮስ በጻፈው እና ሶቅራጥስ እና አውሳብዮስ መዘግበው ባቆዩን ደብዳቤ ላይ ይህ ታሪክ ተገልጧል፡፡
ቀጣዮቹ 300 ዓመታት ለክርስቲያኖች የመከራ ጊዜያት ነበሩ፡፡ የሮም ቄሳሮች ክርስትናን እና ክርስቲያኖችን የሚያሳድዱባቸው ዓመታት በመሆናቸው መስቀሉን የመፈለግ ጉዳይ በልቡና እንጂ በተግባር ሊታሰብ አይችልም፡፡ ዓመታት እያለፉ ሲሄዱም ኢየሩሳሌም እየተዘበራረቀች እና የጥንት መልኳ እየተቀየረ በመሄዱ በጌታ መቃብር ላይም የሮማ አማልክትን ለማክበር ቤተ መቅደስ በመሠራቱ ነገሩ ሁሉ አስቸጋሪ እየሆነ ሄደ፡፡

የመስቀሉ እንደገና መገኘት

ጥንታውያን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎች መስቀሉን እንደገና ያገኘችው ንግሥት ዕሌኒ መሆንዋን ይናገራሉ፡፡ 380 ዓም አካባቢ የተወለደው ታሪክ ጸሐፊው ሶቅራጥስ Ecclesiastical History በተሰኘው መጽሐፉ ላይ በምእራፍ 17 መስቀሉ እንዴት እንደ ተገኘ ዝርዝር መረጃ ይሰጠናል፡፡ ንግሥት ዕሌኒ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዛ በጎልጎታ የጌታ መቃብር ላይ የተሠራውን የቬነስ ቤተ መቅደስ አፈረሰችው፤ ቦታውንም በሚገባ አስጠረገችው፡፡ በዚያን ጊዜም የጌታችን እና የሁለቱ ሽፍቶች መስቀሎች ተገኙ፡፡ ከመስቀ ሎቹም ጋር ጲላጦስ የጻፈው የራስጌው መግለጫ አብሮ ተገኘ፡፡
ሶቅራጥስ ከሦስቱ መስቀሎች አንዱ የክርስቶስ መሆኑን እንዴት ሊታወቅ እንደቻለ ሲገልጥ እንዲህ ይላል «አቡነ መቃርዮስ በማይድን በሽታ ተይዛ ልትሞት የደረሰችን አንዲት የተከበረች ሴት አመጡ፡፡ ሁለቱን መስቀሎችንም አስነኳት፤ ነገር ግን ልትድን አልቻለችም፤ በመጨረሻ ሦስተኛውን መስቀል ስትነካ ድና እና በርትታ ተነሣች፡፡ በዚህም የጌታ መስቀል የትኛው እንደሆነ ታወቀ» ይላል፡፡ ከዚያም ንግሥት ዕሌኒ በጌታ መቃብር ላይ ቤተ ክርስቲያን አሠራች፡፡ ከመስቀሉ የተወሰነውን ክፍል ከፍላ ከችንካሮቹ ጋር ወደ ቁስጥንጥንያ ስትወስደው ዋናውን ክፍል በጎልጎታ ቤተ ክርስቲያን ተወችው፡፡
ይህንን ታሪክ ሄርምያስ ሶዞሜን የተባለው እና 450 ዓም አካባቢ ያረፈው ታሪክ ጸሐፊም Ecclesiastical History, በተሰኘው ጥንታዊ መጽሐፉ በክፍል ሁለት ምእራፍ አንድ ላይ ይተርከዋል፡፡ ዞሲማን እንደሚለው 325 ዓም የተደረገው ጉባኤ ኒቂያ ሲጠናቀቅ የቆስጠንጢኖስ ትኩረት ወደ ኢየሩሳሌም ዞረ፡፡
ምንም እንኳን ሶዞሜን ባይቀበለውም መስቀሉ የተቀበረበትን ቦታ ያመለከተው ከከተማዋ በስተ ምሥራቅ ይኖር የነበረ አንድ አይሁዳዊ መሆኑን እና እርሱም ይህንን መረጃ ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ ከነበረ መዝገብ ማግኘቱን እንደ ሰማ ጽፏል፡፡ ንግሥት ዕሌኒ ባደረገችው አስቸጋሪ ቁፋሮ መጀመርያ ጌታ የተቀበረበት ዋሻ፤ ቀጥሎም ከእርሱ እልፍ ብሎ ሦስቱ መስቀሎች መገኘታቸውን ሶዞሜን ይተርካል፡፡ ከመስቀሎቹም ጋር የጲላጦስ ጽሑፍ አብሮ መገኘቱን እና የጌታ መስቀል ከሌሎች የተለየበትን ሁኔታ ከሶቅራጥስ ጋር ተመሳሳይ በሆነ ሁኔታ ይተርከዋል፡፡ ንግሥት ዕሌኒ በጎልጎታ፣ በቤተልሔም፣ በደብረ ዘይት፣ አብያተ ክርስቲያናትን አሠርታ በሰማንያ ዓመቷ እንዳረፈች ሶዞሜን ይተርካል፡፡ ብዙ የታክ ጸሐፊዎች ዕረፍቷን 328 ዓም አካባቢ መስቀሉ የተገኘ በትንም 326 ዓም ያደርጉታል፡፡ 457 ዓም አካባቢ ያረፈው ቴዎዶሮት የተባለው ታሪክ ጸሐፊም የመስቀሉን የመገኘት ታሪክ ተመሳሳይ በሆነ መንገድ ያቀርበዋል፡፡

መስቀሉ በኢየሩሳሌም

ንግሥት ዕሌኒ ለበረከት ያህል የተወሰነ ክፍል ወደ ቁስጥንጥንያ ከመውሰዷ በቀር አብዛኛውን የመስቀሉን ክፍል በብር በተሠራ መሸፈኛ አድርጋ በጎልጎታ ቤተ ክርስቲያን እንዲቀመጥ ለአቡነ መቃርዮስ ሰጥታቸዋለች፡፡ ይህ መስቀል በየተወሰነ ጊዜ እየወጣ ለምእመናኑ ይታይ እንደ ነበር አንዳንድ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ 380 ዓም ኤገርያ የተባለች ተሳላሚ መነኩሲት ቅዱስ መስቀሉ ወጥቶ በተከበረበት በዓል ላይ ተገኝታ ያየችውን ለመጣችበት ገዳም ጽፋ ነበር፡፡ /M.L. McClure and C. L. Feltoe, ed. and trans. The Pilgrimage of Etheria, Society for Promoting Christian Knowledge, London, (1919)/
አንዳንድ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት የመስቀሉ ክፍልፋዮች ወደ ተለያዩ ሀገሮች መወሰድ የጀመሩት በዚህ ጊዜ ነው፡፡ በሞሪታንያ ቲክስተር በተባለ ቦታ የተገኘውና 359 ዓም አካባቢ የተጻፈው መረጃ የመስቀሉ ክፍልፋዮች ቀደም ብለው ወደ ሌሎች ሀገሮች መግባት እንደ ጀመሩ ያሳያል፡፡ ቄርሎስ ዘኢየሩሳሌም መስቀሉ ከተገኘ ከሃያ አምስት ዓመታት በኋላ 348 ዓም በጻፈው አንድ ጽሑፍ ላይ «ዓለሙ በሙሉ በጌታችን መስቀል ክፍልፋዮች ተሞልቷል» በማለት ገልጦ ነበር፡፡ ከዚህም ጋር «ዕጸ መስቀሉ እየመሰከረ ነው፡፡ እስከ ዘመናችንም ድረስ ይኼው እየታየ ነው፡፡ ከዚህ ተነሥቶም በመላው ዓለም እየተሠራጨ ነው፡፡ በእምነት ክፍልፋዮቹን እየያዙ በሚሄዱ ሰዎች አማካኝነት» ብሏል፡፡/On the Ten Points of Doctrine, Colossians II. 8./
ዮሐንስ አፈ ወርቅም የመስቀሉን ቅንጣቶች ሰዎች በወርቅ በተሠራ መስቀል ውስጥ በማድረግ ምእመናን በአንገታቸው ላይ ያሥሩት እንደ ነበር ጽፏል፡፡ በዛሬዋ አልጄርያ በቁፋሮ የተገኙ ሁለት ጽሑፎች የመስቀሉ ክፍልፋዮች 4ኛው መክዘ የነበራቸውን ክብር ይናገራሉ፡፡ /Duval, Yvette, Loca sanctorum Africae, Rome 1982, p.331-337 and 351-353/፡፡ 455 ዓም በኢየሩሳሌም የነበረው ፓትርያርክ ለሮሙ ፖፕ ለልዮን የመስቀሉን ቁራጭ እንደ ላከለት ተመዝግቧል፡፡
በአውሮፓ ምድር የተዳረሰው አብዛኛው የመስቀሉ ክፍልፋይ የተገኘው ከባዛንታይን ነው፡፡ 1204 ዓም በአራተኛው የመስቀል ጦርነት ጊዜ የዘመቻው ተካፋዮች በዓረቦች ጦር ድል ሲመቱ ፊታቸውን ወደ ቁስጥንጥንያ አዙረው ከተማዋን፣ አድባራቱን እና ገዳማቱን ዘረፏቸው፡፡ በዚያ ጊዜ ተዘርፈው ከሄዱት ሀብቶች አንዱ ዕሌኒ ከኢየሩሳሌም ያመጣችው የመስቀሉ ግማድ ነበር፡፡ ይህንን ግማድ እንደ ገና በመከፋፈል አብዛኞቹ የአውሮፓ አብያተ ክርስቲያናት ሊዳረሱት ችለዋል፡፡ የወቅቱን ታሪክ ከመዘገቡት አንዱ ሮበርት ክላሪ «በቤተ መቅደሱ ውስጥ አያሌ ውድ ንዋያት ይገኙ ነበር፡፡ ከእነዚህም መካከል ከጌታ መስቀል የተቆረጡ ሁለት ግማዶች ነበሩ፡፡ ውፍረታቸው የሰው እግር ያህላል፤ ቁመታቸውም ስድስት ጫማ ይህል ነበር» ብሏል፡፡ /Robert of Clari's account of the Fourth Crusade, chapter 82: OF THE MARVELS OF CONSTANTINOPLE/

የመስቀሉ ለሁለተኛ ጊዜ መጥፋት

እስከ ስድስተኛው መክዘ ድረስ በኢየሩሳሌም ጎልጎታ የነበረው መስቀል 614 ዓም በፋርሱ ንጉሥ ክሮስረስ 2 /Chrosroes II/ ተወሰደ፡፡ የፋርሱ ንጉስ ኢየሩሳሌምን በወረረ መስቀሉን እና ፓትርያርክ ዘካርያስን ማርኮ ወደ ፋርስ ወሰዳቸው፡፡ እንደ ገና ወደ ኢየሩሳሌም የተመለሰው ሕርቃል 627 ዓም ባደረገው ጦርነት ክሮስረስ ድል ሲሆን ነው፡፡ ሕርቃል በመጀመርያ ወደ ቁስጥንጥንያ ካመጣው በኋላ እንደ ገና ወደ ኢየሩሳሌም ወስዶ በቀድሞ ቦታው በጎልጎታ አስቀምጦት ነበር፡፡
እስከ አሥረኛው መክዘ ድረስ በኢየሩሳሌም በቀድሞ ክብሩ ቢቆይም ዐረቦች አካባቢውን እየተቆጣጠሩ ሲመጡ በኢየሩሳሌም የሚኖሩት ክርስቲያኖች መስቀሉን 1009 ዓም አካባቢ ሠወሩት፡፡ 90 ዓመታት ያህል ያለበት ቦታ ተሠውሮ ከኖረ በኋላ በመጀመርያው የመስቀል ጦርነት ጊዜ 1099 ዓም ከተሠወረበት ወጥቶ እንደ ቀድሞው መታየት ጀመረ፡፡

ለሦስተኛ ጊዜ መጥፋት

1187 ዓም በሐቲን ዐውደ ውጊያ ሳላሕዲን የተባለው የዓረቦች የጦር መሪ የመስቀል ጦረኞችን ድል አድርጎ ኢየሩሳሌምን ሲቆጣጠር በዚያ የነበረውን መስቀል መውሰዱን አንዳንድ የታሪክ መዛግብት ይገልጣሉ፡፡ ከዚያ በኋላ ግን መስቀሉ የት እንዳለ እስካሁን ማረጋገጥ አልተቻለም፡፡ በወቅቱ የነበሩት የሮም ነገሥታት መስቀሉን ለማግኘት ከሳላሕዲን ጋር ብዙ ድርድር አድርገው ሳይሳካላቸው ቀርቷል፡፡
በአብዛኞቹ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ የመስቀሉ ክፍልፋይ እንዳለ ሁሉም ይናገራሉ፡፡ አንዳንዶቹ አለ የሚባለው ክፍልፋይ ከመብዛቱ የተነሣ የሚያነሡት ትችት አለ፡፡ ጆን ካልቪን «ሁሉም ክፍልፋዮች ከመስቀሉ የወጡ ከሆነ፤ እነዚህን ሁሉ ብናሰባስባቸው አንድ መርከብ የግድ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ወንጌል ግን ይህንን መስቀል አንድ ሰው እንደ ተሸከመው ይነግረናል» ብሎ ነበር፡፡ ይህንን የካልቪንን ሂስ በተመለከተ መልስ የሰጠው ራውል ፈሌውሪ /Rohault de Fleury,/ 1870 ዓም በዓለም ላይ አሉ በሚባሉት የመስቀል ክፍልፋዮች ላይ ጥናት አድርጎ ነበር፡፡ ራውል መጀመርያ የት ምን ያህል መጠን እንዳለ ካታሎግ አዘጋጀ፤ ከዚያም መጠናቸውን አንድ ላይ ደመረ፡፡ በታሪክ እንደሚነገረው የመስቀሉ ክብደት 75 ኪሎ፣ ጠቅላላ መጠኑም 178 ኪዩቢክ ሜትር ነው፡፡ ራውል ያገኛቸውና አሉ የተባሉት ክፍልፋዮች አንድ ላይ ቢደመሩ .004 ኪዩቢክ ሜትር /3.‚942‚000 ኪዩቢክ ሚሊ ሜትር/ ነው፡
በዚህም መሠረት ቀሪው 174 ኪዩቢክ የሚያህለው ሜትር የመስቀሉ ክፍል ጠፍቷል ማለት ነው ብሏል፡፡ /Mémoire sur les instruments de la Passion, 1870/

ግማደ መስቀሉ በኢትዮጵያ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መዛግብት እንደሚሉት ግማደ መስቀሉ ወደ ኢትዮጵያ የገባው 14ኛው መክዘ በዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ነው፡፡ በግሼን አምባ የተቀመጠው ደግሞ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ዘመነ መንግሥት ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን ወደ ኢየሩሳሌም ያደርጉ የነበረውን ጉዞ፣ የኢትዮጵያ ነገሥታት የነበራቸውን ታዋቂነት እና ወደ ሀገረ ናግራን ተጉዘው የሠሩትን ሥራ ስንመለከት ኢትዮጵያ እስከዚያ ዘመን ድረስ ግማደ መስቀሉን ለማግኘት ትዘገያለች ብሎ ለማሰብ ይከብዳል፡፡ በኢየሩሳሌም የሚገኘው የኢትዮጵያ ገዳም መስቀሉ ለወጣበት ቦታ እና ለጎልጎታ ያለውን ቅርበት፤ ዐፄ ካሌብም ከናግራን ዘመቻ በኋላ ዘውዳቸውን ለጎልጎታ ቤተ ክርስቲያን መላካቸውን ስናይ ይህንን የመሰለ ቅዱስ ንዋይ ኢትዮጵያውያን እስከ 13ኛው መክዘ ድረስ አንዱን ክፋይ ሳያገኙት ቆዩ ለማለት ያስቸግራል፡፡ ኤርትራ ውስጥ ግማደ መስቀሉ አለበት የሚባል አንድ ገዳም መኖሩን ሰምቻለሁ፡፡
ክርስትና ብሔራዊ ሃይማኖት ከሆነ በኋላ ነገሥታቱ በሳንቲሞቻቸው ላይ የመስቀል ምልክት ማድረጋቸው፣ እንደ ንጉሥ አርማሕ ያሉትም በበትረ መንግሥታቸው ላይ መስቀል ማድረጋቸው፤ ከቀደምት ክርስቲያን ነገሥታት አንዱ የሆነው ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል ተብሎ መሰየሙን ስናይ የመስቀሉ ነገር በኢትዮጵያ ውስጥ የነበረውን ቀደ ምት ታሪክ ያመለክተናል፡፡
በዛግዌ ሥርወ መንግሥትም ዐፄ ላሊበላ ስመ መንግሥቱ ገብረ መስቀል መባሉን፣ ሚስቱም ንግሥት መስቀል ክብራ መባሏን፣ ከሠራቸው አስደናቂ ውቅር አብያተ ክርስቲያ ናት አንዱ ቤተጊዮርጊስ  በመስቀል ቅርጽ መሠራቱን ስናይ ኢትዮጵያውያን ከመስቀሉ ጋር ቀድመው መተዋወቃቸውን ያስገምተናል፡፡ በመሆኑም በዚህ ረገድ መዛግብትን የማገላበጥ እና የመመርመር ሥራ የሚቀረን ይመስላል፡፡
በዐፄ ዳዊት ዘመን መጥቶ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ አማካኝነት በግሼን አምባ የተቀመጠው ግማደ መስቀል በይፋ የታወቀውና በነገሥታቱ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት የመጣው ዋናው እንጂ የመጀመርያው ነው ለማለት ያስቸግራል፡፡ ተክለ ጻድቅ መኩርያ ግብጻዊው ጸሐፊ ማክሪዝ Historia Rerum Isi amiticarumin Abissinia በሚለው መጽሐፉ የገለጠውን መሠረት በማድረግ «የኢትዮጵያ ታሪክ ከይኩኖ አምላክ እስከ ልብነ ድንግል» በሚለው መጽሐፋቸው ላይ እንደሚተርኩት አስቀድሞ በሰይፈ አርእድ ዘመን በግብጹ ሡልጣን እና በኢትዮጵያዊው ንጉሥ መካከል የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት የልዑካን ቡድን ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ነበር፡፡ የልዑካን ቡድኑ መሪ የኢየሩሳሌሙ ፓትርያርክ አባ ዮሐንስ ነበሩ፡፡
ልዑካኑ ወደ ኢትዮጵያ ሲደርሱ ያገኟቸው ዐፄ ዳዊትን ነበር፡፡ በሁለቱ ሀገሮች መካከል የነበረውን ችግር በውይይት እና በስምምነት ፈትተው አስማሟቸው፡፡ ዐፄ ዳዊትም ግማደ መስቀሉን እንዲልኩለት የኢየሩሳሌሙን ፓትርያርክ አቡነ ዮሐንስን አደራ አላቸው፡፡ እርሳቸውም ከግማደ መስቀሉ ጋር ሌሎች ንዋያትንም ጨምረው ላኩለት፡፡ በግብጹ ሡልጣን እና በንጉሥ ዳዊት መካከል የተፈጸመው ስምምነት ለኢትዮጵያውያን ተሳላሚዎች እና ነጋዴዎች ጥበቃ ማድረግን የሚያካትት ስለ ነበር ግማደ መስቀሉን የያዙት የዐፄ ዳዊት መልእክተኞች ያለ ችግር ኢትዮጵያ ገቡ፡፡
አንዳንድ የታሪክ መዛግብት ዐፄ ዳዊት ጥቅምት ዘጠኝ ቀን 1404 ዓም በድንገት ሲያርፉ ግማደ መስቀሉ በሱዳን ስናር ነበር ይላሉ፡፡ ከስናር ያነሡት ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ መሆናቸውንም ይተርካሉ፡፡ ተክለ ጻደቅ መኩርያ ግን ዐፄ ዳዊት ወደ ኢትዮጵያ አስገብተውት በተጉለት ውስጥ ቤተ ክርስቲያን ሠርተውለት እንደ ነበር ይናገራሉ፡፡ ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ የነገሡት 1434 ዓም ነው፡፡ በእነዚህ ሠላሳ ዓመታትም አያሌ ነገሥታት ተፈራርቀዋል፡፡ እነዚህ ነገሥታት ግማደ መስቀሉን ለመውሰድ ያልቻሉበትን ምክንያት ማወቅ አይቻልም፡፡ ምናልባት ግን በነበረው የርስ በርስ ሽኩቻ ተጠምደው ይሆናል፡፡ ሌሎች መዛግብት እንጂ በኋላ ዘመን /ምናልባትም በዐፄ ልብነ ድንግል/ የተጻፈው የዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ዜና መዋዕል የግማደ መስቀሉን ነገር አይነግረንም፡፡
ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ግሼን አምባ ላይ ግማደ መስቀሉን ያስቀመጠበት ሁለት ምክንያቶች ይኖራሉ፡፡ የመጀመርያው የአምባው የመስቀለኛ ምልክት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ አምባው በዘመኑ በልዩ የንጉሠ ነገሥቱ ኃይል ይጠበቅ ስለ ነበር ነው፡፡ በግራኝ አሕመድ ወረራ ጊዜም ቢሆን ሌሎች ሀብቶች ከአምባው ላይ መዘረፋቸውን እንጂ የተቀበረውን ለማውጣት ሙከራ መደረጉን የግራኝን ታሪክ የጻፈው ዐረብ ፋቂህ አያነሣም፡፡ ግማደ መስቀሉን የማውጣት ጥረት ተደረገ የሚባለው 1851 ዓም ዐፄ ቴዎድሮስ በጣም የሚወዷቸው ባለቤታቸው እቴጌ ምንትዋብ ከሞቱ ከአንድ ዓመት በኋላ ነው፡፡ ንጉሥ ቴዎድሮስ እቴጌ ምንትዋብን እጅግ ይወዷቸው ስለነበር በመስቀሉ አማካኝነት ከሞት ለማስነሣት አስበው ነበር፡፡ ይህንንም በወታደሮች ኃይል በማስቆፈር አስጀምረውት ነበር፡፡ በመካከል ግን ከጉድጓዱ ኃይለኛ ሽታ እና ጢስ ወጥቶ ከቆፋሪዎቹ የተወሰኑትን በመግደሉ ሃሳባቸውን ሠርዘው ባለቤታቸውን በግሼን አምባ ቀብረው ተመልሰዋል፡፡

ከዳንኤል ክብረት

                                                            ወስብሐት ለእግዚአብሔር

1 comments:

አስተያየት ወይም መልዕክት ካልዎት፤ ከዚህ በታች ያለውን ሰሌዳ ይጠቀሙ።